(ቄሮ ዘጋቢ October 25, 2011) በየቦታዉ ያሉ ካድሬዎችና የገዢው ፓርቲ ቅጥረኞች የአቶ መለስ ዜናዊን የፓርላማ ንግግር ካዳመጡ በኋላ በሰላማዊና ሕገ መንግስቱን እያከበሩ የሚንቀሳቀሱ የመድረክ አባል ድርጅቶችን፣ “ሽብርተኞች ናቸዉ” በሚል የፖሮፖጋንዳ ዘመቻ የከፈቱ ሲሆን፣ የመድረክ አባላትን በየቀበሌዉና በየወረዳዉ የማስፈራራት፣ የማሰር፣ የመግደል ፣ የማወክ ዘመቻቸዉን እንዳጧጧፉ የደረሰን ዜና ያመለክታል።
በደቡብ ጎንደር በመምህርነት ያገለግሉ የነበሩ፣ የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ አባልና ደጋፊ የነበሩት፣ አቶ ሙሳ ኢብራሁም፣ ጥቅምት ስምንት ቀን 2004 ዓ.ም በኢሕአዴግ ታጣቂዎች ተደብድበዉ መሞታቸዉን ከአዲስ አበባ የደረሰን ዘገባ አክሎ ያትታል።
የአንድነት ፓርቲ የምዕራብ ጎጃም ዞን ምክር ቤት አባል የሆኑት ሻምበል የሺዋስ ይሁን፣ ጥቅምት ስድስት ቀን በፌዴራል ፖሊሲ ተይዘዉ ከተወሰዱ በኋላ የት እንደደረሱ ማወቅ እንዳልተቻለም የደረሰን ዜና ያመለክትል። በተመሳሳይ ሁኔታ፣ አቶ ሃብታሙ አያሌዉና ዘመዲያ አገዘ የተባሉ፣ በምስራቅ ጎጃም ነዋሪ የሆኑ የአንድነት ደጋፊ፣ ሰኔ ሃያ አምስት ቀን 2003 ዓ.ም በወረዳዉ ፖሊስ ተይዘው ከተወሰዱ ጀምሮ ቤተሰቦቻቸዉ የት እንዳሉ ለማወቅ እንዳልቻሉ ዜናዉ አክሎ ይገልጻል።
ሐምሌ 13 ቀን 2003 ዓ.ም አሁንም በምስራቅ ጎጃም የሚገኝ የወረዳ ፍርድ ቤት፣ በአቶ አያል ጌታነህ ላይ ኢፍትሃዊ በሆነ መንገድ፣ ለአንድ አመት ከሕብረ ተሰቡ ጋር እንዳይገናኙ የወሰነ ሲሆን ፣ አቶ አያል ጌታነህ በአሁኑ ወቅት በፍርሃትና በትልቅ ወከባ ላይ እንደሚገኙም ለማወቅ ችለናል።
ከጎጆምና ከጎንደር ወደ ሰሜን አለፍ ስንል፣ በትግራይም፣ ዜጎች በብዛት እየታሰሩ እንደሆነም ለማረጋገጥ ችለናል። የመድረክን አላማ የያዘ ወረቀት ለህዝብ ሲያሰራጩ የነበሩት የአረና አባል፣ አቶ አያሌዉ በየነ በሽሬ ተይዘዉ የታሰሩ ሲሆን፣ መምህር ጎይቶም ጸጋዬ የአረና አባል ስለሆኑ ከስራቸዉ ተባረዋል።
አቶ አማረ ተወልደ የተባሉ የአረና አባል፣ እርሳቸዉም በሁመራ የመድረክን አላማ ወረቀት ለሕዝብ ሲያሰራጩ በአማራዉ ክልል ፖሊሶች ተይዘዉ፣ “አረናዎች በትግራይ እንጂ በአማራዉ ክልል መንቀሳቀስ አይችሉም” በሚል ለበርካታ ቀናት እንደታሰሩ የደረሰን ዜና ያመለክታል።
ላለፉት ሶስት ወራት ገዢዉ ፓርቲ ሽብርተኖች ናቸው እያለ ኦሮሚያን የአማራዉን የትግራይ ክልል ጨምሮ በመላዉ አገሪቷ ግዛቶች ከፍተኛ የሆነ ዜጎችን የማወክ ተግባር እየፈጸመ ሲሆን፣ አቶ አንዱዋለም አርጌ፣ አቶ እስክንደር ነጋን ጨመሮ እጅግ በጣም ብዛት ያላቸዉ ሰላማዊ ዜጎች እንዳሰረ የሚታወቅ ነዉ።