ቦሩ በራቃ | July 29,2014
የሰው ለ ሰውን ድራማ እስከ መጨረሻው (ክፍል 140) ድረስ ተከታተልኩት። እንደ ብዙዎቹ ሁሉ እኔም የኣቶ እስናቀ ኣሸብርን መጨረሻ ለማየት በጥቂቱም ቢሆን መጉዋጉዋቴ ኣልቀረም። በድራማው የትወና ድር ሁሉም ቅርንጫፎች በስተጀርባ ብቸኛውና ቀንደኛው ጠላት ተደርጎ የተፈረጀውን እስናቀ ኣሸብር! ይህ ድራማ ከተጀመረበት ወቅት ኣንስቶ የኣስናቀን የትወና ሚናና ብቃት የተከታተሉት ኣንዳንድ ወገኖች ድራማውን በፖለቲካ መነጽር ሲቃኙት ከመለስ ዜናዊ ኣምባገነንነትና ብልጣብልጥነት ጋር ያገናኙታል። ለኔ ግን ይህ ኣይዋጥም። በፖለቲካ መነጽር ድራማውን እንቃኘው ከተባለ እኔ የኣስናቀን ሚና የማስቀምጠው በሌላ መልኩ ነው። እስናቀ በድራማው ውስጥ የተሳለው ከኣምባገነንነቱ ይልቅ በስግብግብነቱ ነው። በብልጣብልጥነቱም ሳይሆን ራሱን ብልጥ ኣድርጎ የሚያስብ ነገር ግን በውስጣዊ ማንነቱ ቂል ተደርጎ ነው። በኣጭሩ ይህ ኣስናቀ የተባለው ግለሰብ ሞኝና ስግብግብ ነው።
ይህ ደግሞ ብዙዎቹ ኣቢሲኒያዊ ፖለቲከኞች የኦሮሞን ብሄረተኝነት የሚተረጉሙበት የተለመደ ምስል ነው። ኦሮሞዎች ኦሮምያ የኦሮሞ ናት በማለታቸው ብቻ በኣቢሲኒያዊያኑ ፖለቲከኞች ዘንድ ስግብግብ ተደርገው ይታያሉ። ኦሮሞ ምንም በብዙህነቱና ኢኮኖሚያዊ ኣቅሙ ልቆ የወጣ ህዝብ ቢሆንም እነርሱ ዘንድ ሁሌም እንደ ቂል ይቆጠራል። ኦሮሞ በጭንቅላቱ ብስለት ሳይሆን በጡንቻው ኣቅም የሚያስብ ተደርጎ ይተረጎማል። ተማረ ኣልተማረ ኦሮሞ ስልጡን ሊሆን ኣይችልም እያሉም የሚያንቁዋሽሹትና የሚሳለቁበት ቁጥራቸው ቀላል ኣይደለም።
ሰው ለ ሰው ድራማ ውስጥ ለኣስናቀ ኣሸብር (ኣበበ ባልቻ) የተሰጠው የትወና ሚናም ከዚህ የፖለቲካችን እውነታ ጋር የሚመሳሰልበት መልኩ ብዙ ነው። ገና ሲጀመር ኣስናቀ ኣሸብር ‘እሸባሪ’ ተደርጎ ነው የተሳለው። የኦሮሞ ህዝብ ብሄርተኝነትም ከኦነግ ጋር ተያይዞ በእሸባሪነት እንደሚፈረጅ ልብ ይሏል። የኣስናቀ እሸብርን ባህሪይ ተላብሶ የሚጫወተው ተዋናዩ ኣበበ ባልቻ ራሱ በድራማው ውስጥ እስከ መጨረሻው ድረስ ሚናቸውን ይዘው ከዘለቁት ተዋናዮች መካከል ብቸኛው ኦሮሞ ነው። የጋሽ ኣስኒ ብሶት የሚጀምረው ከኣንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ህይወቱ ነው። የድሃ ቤተሰብ ልጅ ነበረ። ሁሌም በትምህርት ቤት ጉዋደኞቹ መሃል ብቸኛው የበይ ተመልካች ነበረ። በልጅነቱ ከነ መስፍን ጋር ሚኒስትሪ ተፈትኖ ፈተና ወደቀ። እነ መስፍን ፈተና ኣለፉ። ፈተና በወደቀው ኣስናቀ ላይም ተሳለቁበት። ኣስናቀ በወቅቱ የሁሉም ልጆች መሳለቂያ መሆኑ በእጅጉ ኣማርሮት ነበር። ነገር ግን በድራማው ኣብዛኛው ክፍሎች ውስጥ ደጋግሞ ስሙን ሲያነሳው የሰማነውና የኣፋን ኦሮሞ ተረቶችን ልቅም ኣድርጎ ያስተማረው ኣሳዳጊ ኣጎቱ ነበር በኣጭር ምክር ያረጋጋው።